settings icon
share icon
ጥያቄ፤

በውኑ እግዚሐብሔር አለን? እግዚሐብሔር እንዳለ በምን ላረጋግጥ እችላለሁ?

መልስ፤


እግዚሐብሔር እንዳለ እናውቃለን። ምክንያቱም ራሱን ለኛ በሦስት መንገዶች ገልጦልናል። ይኸውም በፍጥረት፣ በቃሉና በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ነው።

ለእግዚሐብሔር ህልውና መሰረታዊ ማስረጃ በቀላሉ የሠራውን መመልከት ነው። “ከዓለም መፈጠር ጀምሮ የእግዚሐብሔር ባህሪያት ማለትም ዘላለማዊ ኃይሉና መለኮታዊ ተፈጥሮው በግልፅ ታይቷል። ከተሠራውም ግንዛቤ (መረዳት) ተገኝቷል። ስለዚህ ሰዎች ምክንያት የላቸውም”(ሮሜ 1፡ 20)። “ሰማያት የእግዚሐብሔርን ክብር ይናገራሉ፣ የሰማይ ጠፈር የእጁን ሥራ ያወራል”(መዝሙር 19፡ 1)።

የእጅ ሰዓት በአውላላ ሜዳ መካከል ወድቆ ባገኝ “የታየው” ከየትም ነው ወይም ሁልጊዜም እዛው ነበር ማለት አልችልም። የሰዓቱን ሥሪት ተመርኩዤ የሰራው ሰው እንዳለ እገምታለሁ። በዙሪያችን ባለው ዓለም ግን በእጅጉ ታላቅ የሆነ ቅርፅና ትክክለኛነት አለ። የኛ የጊዜ አለካክ በእጅ ሰዓቶች ላይ የተመሰረተ አይደለም። ነገር ግን የእግዚሐብሔር ሥራ በሆነው የመሬት መደበኛ ሽክርክሪት ነው። ፍጥረተ ዓለም የረቂቅ ሥራ ማሳያ ሲሆን ታላቅ የሆነ ሞዴል አውጪም እንዳለ ማረጋገጫ ነው።

ለምሳሌ ያህል ሚስጢራዊ የሆነ መልዕክት ባገኝ ምስጢሩን የሚፈታልኝ ባለሙያ እፈልጋለሁ። ምስጢራዊ መልዕክቱን የፈጠረው አዋቂ ላኪ ይኖራል ብዬ እገምታለሁ። በሰውነታችን ውስጥ በተሸከምነው በእያንዳንዱ ሕዋስ ያለው ውስብስብ የዲኤን.ኤ. “ምስጢር” አይደንቅም! የዲኤን.ኤ ውስብስብነትና ተግባር የምስጢራዊ መልዕክቱን አዋቂ ፀሐፊን አያመለክተንም? እግዚሐብሔር አስደናቂና እርስ በራሱ የተስማማ ዓለም መሥራቱ ብቻ ሳይሆን በእያንዳንዱ ሰው ልብ ዘላለማዊነትን ፈጥሯል። (መፅሐፈ መክብብ 3፡11)። የሰው ልጅ በአይን ከሚታየው ውጪ ሕይወት ድብቅ እንደሆነ በውስጡ ይገነዘባል። ከዚህ ዓለም የተለምዶ ድግግሞሽ የላቀ ከፍተኛ ሕልውና እንዳለ ያምናል። የኛ የዘላለማዊነት ስሜት ራሱን ቢያንስ በሁለት መንገድ ገልጧል፣ በሕግ ማውጣትና በአምልኮ።

በታሪክ ውስጥ የታየው እያንዳንዱ ሥልጣኔ የተወሰኑ የሞራል ሕጎችን ሲያከብር ይታያል። አስደናቂው ነገር ግን ከባህል ወደ ባህል ተመሳሳይነት ይታይባቸዋል። ለአብነት ያህል የፍቅር ሐሳብ ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ሲኖረው ውሸት ግን በተፃራሪው የተወገዘ ነው። ይህ የሞራል ግንዛቤ ትክክል ወይም ስህተት ነው የምንለው አስተሳሰብ እነዚህን ሕጎች የሰጠን ከፍተኛ የሞራል ባለቤት እንዳለ ይጠቁመናል።

በተመሳሳይ መልኩ በዓለም ዙሪያ ያሉ ሕዝቦች ባህላቸው ምንም ይሁን ምን የአምልኮ ሥርዓት አበጅተዋል። የሚመለከው ነገር ሊለያይ ቢችልም “ከፍተኛ ኃይል” መኖሩ ግን የማይካድ የስብዕና አካል ነው። ለአምልኮ ያለን ዝንባሌ እግዚሐብሔር “ሰውን በመልኩ ፈጠረ” ከሚለው እውነታ ጋር ይጣጣማል።(ዘፍጥረት 1፡ 27)። እግዚሐብሔር በተጨማሪ በቃሉ በመፅሐፍ ቅዱስ ራሱን ለኛ ገልጧል። በመፅሐፍ ቅዱስ በሙሉ የእግዚሐብሔር ህልውና እንደተጨባጭ ሐቅ ተወስዷል።(ዘፍጥረት 1፡1፣ ዘፀአት 3፡14)። ቤንጃሚን ፍራንክሊን የራሱን የሕይወት ታሪክ ሲፅፍ የራሱን ህልውና ለማረጋገጥ ጊዜ አላባከነም። በተመሳሳይ መልኩ እግዚሐብሔርም በመፅሐፉ ውስጥ የራሱን ህልውና ለማረጋገጥ ብዙጊዜ አላጠፋም። ሕይወት ለዋጭ የሆነው የመፅሐፍ ቅዱስ ባህርይ፣ ተአማኒነቱና የተከተሉት ተዓምራቶች በቅርበት እንድንመለከተው ግድ ይለናል።

እግዚሐብሔር ራሱን የገለጠበት ሦስተኛ መንገድ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ነው። (ዮሐንስ 14፡ 6-11) “በመጀመሪያ ቃል ነበር፣ ቃልም በእግዚሐብሔር ዘንድ ነበር፣ ቃልም እግዚሐብሔር ነበር። “ቃልም ሥጋ ሆነ፣ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፣ አንድ ልጅም በአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነውን ክብሩን አየን።” (ዮሐንስ 1፡14)።

በአስደናቂው የኢየሱስ ሕይወት ሙሉ የብሉይ ኪዳንን ሕግ ጠብቋል። መሲሑን የተመለከቱትን ትንቢቶች ፈፅሟል።( ማቴዊስ 5፡17)። ሥፍር ቁጥር የሌላቸው የርህራሄ ድርጊቶችን አከናውኗል። ለፈጣሪነቱ ምስክር እንዲሆንና መልዕክቱንም ለማረጋገጥ ሕዝባዊ ተዓምራቶችን አሳይቷል። (ዮሐንስ 21፡ 24-25)። ከዚያም በተሰቀለ በሦስተኛው ቀን ከመቃብር ተነስቷል። ይህን እውነት በመቶዎች የሚቆጠሩ የዓይን ምስክሮች አረጋግጠውታል። (1ኛ ቆሮንቶስ 15፡ 6)። የታሪክ መዛግብት ክርስቶስ ማን እንደሆነ “በማስረጃ” የተሞሉ ናቸው። ሐዋርያው ጳውሎስ እንደተናገረው “ይህ በስውር የተደረገ አይደለምና”። (የሐዋሪያት ሥራ 26፡26)።

እግዚሐብሔርን በሚመለከት የራሳቸው ሐሳብ ያላቸው ተጠራጣሪዎች ማስረጃውን እንደፈለጉ እንደሚያነቡት እንገነዘባለን። አንዳንዶች ደግሞ የቱንም ያህል ማስረጃ ቢቀርብ አምነው የማይቀበሉ ይኖራሉ። (መዝሙር 14፡ 1)። ሁሉም ነገር ዞሮዞሮ በእምነት ላይ ያርፋል።(ዕብራውያን 11፡ 6)።

English



ወደ አማርኛ መነሻ ገጽ ለመመለስ

በውኑ እግዚሐብሔር አለን? እግዚሐብሔር እንዳለ በምን ላረጋግጥ እችላለሁ?
© Copyright Got Questions Ministries